የሰማያዊ ሊቀመንበር መቀመጫቸውን አ.አ ላደረጉ 21 የአውሮፓ ህብረት ሀገራት ተወካዮች ገለጻ አደረጉ

 

1044212_856562327802760_3735872674734306429_nየሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት መቀመጫቸውን በአዲስ አበባ ላደረጉ 21 የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት ተወካዮች በኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ገለጻ ማድረጋቸውን ገለጹ፡፡

ሊቀመንበሩ ዛሬ መጋቢት 6/2008 ዓ.ም በአዲስ አበባ የአውሮፓ ህብረት ጋባዥነት በተለያዩ የሀገሪቱ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ማብራሪያ የሰጡ ሲሆን፣ በተለይ በኦሮሚያ፣ ጋንቤላ፣ ደቡብ ኦሞ፣ ኮንሶ እና ወልቃይት አካባቢዎች ስለተከሰቱ ህዝባዊ የተቃውሞ እንቅስቃሴዎች ለተወካዮቹ ገለጻ ማድረጋቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ ተናግረዋል፡፡

በኢትዮጵያ የአውሮፓ ህብረት ምክትል ኃላፊ ተርሂ ሌተነን በመሩት ገለጻ ላይ ሊቀመንበሩ ኢ/ር ይልቃል በኢትዮጵያ ስላለው የፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ማህበራዊ ቀውሶች ላይ ማብራሪያ መስጠታቸውን ገልጸዋል፡፡ በዚህም በሀገሪቱ በአሁኑ ወቅት 18 ሚሊዮን ዜጎች ለርሃብ መዳረጋቸውን፣ የኑሮ ውድነት መጨመሩን፣ ሙስና መንሰራፋቱን፣ የገቢ አለመመጣጠን መጉላቱን እና የስራ አጥነት ችግር እየከፋ መሄዱን ለተወካዮች መግለጻቸውን ተናግረዋል፡፡

በፖለቲካው መስክም ኢትዮጵያ ውስጥ መድብለ ፓርቲ ፖለቲካ ጨርሶ መዘጋቱን፣ ፓርቲዎች በጸረ-ሰላምነት ተፈርጀው በመንግስት እየተሰለሉ መሆናቸውን በፍርድ ቤት የቀረበ ማስራጃ ማረጋገጡን፣ የሰማያዊ እና መድረክ ፓርቲዎች አባላት በግፍ እስር ላይ መሆናቸውን እንዳብራሩ ለነገረ ኢትዮጵያ አስረድተዋል፡፡

በኦሮሚያ ክልል ህዝቡ መብቱን ለመጠየቅ ለተቃውሞ መውጣቱን ተከትሎ በአራት ወራት ጊዜ ብቻ በመንግስት ከ260 ሰዎች በላይ መገደላቸውን በዝርዝር እንዳስረዱ ሊቀመንበሩ ገልጸዋል፡፡ በወልቃይት የማንነት ጥያቄ አለን በሚል ለትግራይ ክልል እና ለፌደሬሽን ም/ቤት ህጉን ተከትለው ጥያቄ ያነሱ ዜጎች መታሰራቸውንና በመንግስት ሚዲያዎች ግጭት ቀስቃሽ ዘገባ እየቀረበ እንደሆነ መታዘባቸውን፣ ይሄም እንደሚያሳስባቸው ለተወካዮች ማብራራታውን ተናግረዋል፡፡

በመሆኑም ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ችግሮች ከኢህአዴግ በላይ በመሆናቸው መንግስት ሁሉም ፓርቲዎች፣ የማህበራት ተወካዮች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና ሌሎች የሚሳተፉበት አካታች ውይይት እንዲደረግ እንዲፈቅድ ጥሪ ማቅረባቸውንና የህብረቱ ሀገራትም ይህ እንዲሆን አስፈላጊውን ግፊት እንዲያደርጉ ማሳሰባቸውን አስረድተዋል፡፡