በአዲስ አበባ ተደርጎ ያልተሳከው እና የአዛዦች የእርስበርስ ግጭትን ጨምሮ የተጠናቀቀው የፌዴራል ፖሊስ ስብሰባ በባህር ዳር በድጋሚ ተደርጓል፡፡ ስብሰባው የተከወነው ከየካቲት 13-16 ሲሆን ይኽም እንደ አዲስ አበባው ስብሰባ በግጭት እና በጭቅጭቅ ታጅቦ ያለ ውጤት ተበትኗል፡፡ በስብሰባዎቹ ላይ ህዝባዊ ቁጣዎች በስፋት የተነሱ ሲሆን፤ “ህዝቡ መንግስትን ለምን ጠላው? መንግስት ህዝብን ለምን ያሰቃያል? ለምን ህዝባችንን ግደሉ እንባላለን? ወደ ህዝባችን እንድንተኩስ ለምን እንታዘዛለን?” የሚሉ ጥያቄዎች እየተነሱ ዱላ ቀረሽ ጭቅጭቅን ፈጥረዋል፡፡
እያንዳንዱ ህዝባዊ ቁጣን ለምን በጠብ መንጃ እናስታግሳለን? ይህ ትልቅ ስህተት ነው ብለው፤ በርካታ የፌዴራል ፖሊስ አባላት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ የፌዴራል ፖሊስ አዛዦችን ለመደብደብ የሞከሩ አባላት እንደነበሩ የሚገልፁ መረጃዎች ሁሉ ወጥተዋል፡፡ ከስብሰባው በኋላ አራት በከፍተኛ ስልጣን ያሉ የፌዴራል ፖሊስ አባላት መክዳታቸው የታወቀ ሲሆን እስካሁን የት እንደ ደረሱ አልታወቀም፡፡ አባላቱ ለኢትዮጵያ ዲሞክራሲ እና ነፃነት የሚታገሉትን ኃይሎች ለመቀላቀል ወደ ሰሜን ተጉዘዋል ተብለው ተጠርጥረዋል፡፡